ኢንተርፕራይዙ ተኪ ምርቶች ማምረት ላይ አበረታች ውጤት ማሳየቱን ቦርዱ ገለጸ።
የኢንስቲትዩቱ ቴክኖቢዚያ የኢንዱስትሪ ውጤቶች ልማት ኢንተርፕራዝ የሥራ አመራር ቦርድ የኢንተርፕራይዙን የስራ እንቅስቃሴ በመገምገም ውሳኔዎችን አስተላልፏል። በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ቴክኒክና ሙያ ስልጠና ኢንስቲትዩት ዋና ዳይሬክተር ዶ/ር ብሩክ ከድር ሰብሳቢነት ሦስት አጀንዳዎች ላይ የተወያየው ቦርዱ የአፈጻጸም ውሳኔም አስተላልፏል። ዶ/ር ብሩክ ኢንተርፕራይዙ የቦርዱን ውሳኔዎች በትኩረት ለቅሞ እየፈጸመ መሆኑ የሚያበረታታ ነው ብለዋል፡፡ ኢንተርፕራይዙ ተኪ ምርቶችን ለማምረት እየሠራ ያለው ስራ አበረታች መሆኑን የገለጹት ሰብሳቢው ተጠናረው እንዲቀጥሉ ራሱን እያስተዋወቀ መቀጠል እና ፕሮጀክቶችን ማፈላለግ እንደሚገባ ጨምረው ገልፀዋል፡፡ ኢንተርፕራይዙ ሲቋቋም ከያዛቸው ግቦች መካከል ስልጠናን ከምርት ጋር ለማስተሳሰር የተሄደበት ርቀት በጥንካሬ የታዩ እንደሆኑ ሰብሳቢው ገልጸዋል፡፡ የኢንስቲትዩቱ የቴክኖሎጂና ኢንተርፕራይዝ ልማት ም/ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ ጸዳለ ተክሉ ኢንተርፕራይዙ ከልምምድ ወጥቶ ተወዳዳሪ እየሆነ የመጣ ኢንተርፕራይዝ መሆኑን ገልጸው አሁንም ይበልጥ ተጠናክሮ ለመውጣት ማቀድ ይገባል ብለዋል፡፡ ፕሮጀክቶችን በፍጥነት እና በጥራት መፈጸም ላይ ይበልጥ ትኩረት ተደርጎ ሊሰራ እንደሚገባ አንስተዋል፡፡ ይህ ዓመት የኢንስቲትዩቱ የስትራቴጂክ ዓመቱ ማብቂያ በመሆኑ የኢንተርፕራይዙ ስኬት ለኢንስቲትዩቱ ስትራቴጂክ ዓመቱን ስኬት አንዱ ተጨማሪ ፋይዳ እንደሚኖረው ም/ዋና ዳይሬክተሯ ገልጸዋል፡፡ የኢንተርፕራይዙ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ለሚ ቱጆ ያለፋትን ወራት አፈጻጸም ሪፖርት አቅርበው ቦርዱ በኢንተርፕራይዙ ስራ አፈጻጸም መቀጠል ስላሉባቸውና መሻሻል ስለሚገቡ ነገሮች ዝርዝር ውይይት ተደርጓል። ቦርዱ በሁለተኛ አጀንዳነት በውጭ ኦዲት የተሰራውን ሪፖርት አዳምጦ አጽድቋል። በሦስተኛነት ኢንተርፕራዙ ኢንስቲትዩቱን መደጎም በሚያስችለው አማራጭ ላይ በቀረበው ሰነድ ቦርዱ የተወያየ ሲሆን ገንቢ ሀሳቦችን በማከል በአገሪቱ የከፍተኛ ትምህርትና ስልጠና ተቋማትን ለማስተዳደር በወጣው ህግ መሰረት ተግባራዊ እንዲደረግ በውሳኔው አጽቋል። የቦርዱ ሰብሳቢ ዶ/ር ብሩክ ከድር በመጨረሻም ኢንተርፕራይዙ ተኪ ምርት ላይ በቀጣይም ይበልጥ ትኩረት አድርጎ እንዲሰራ፣ የገበያ ትስስር እንዲፈጥር፣ የ21ኛው ክ/ዘመን ት/ቤትን የማስተዳደር ሥራው በትኩረት ሊሰራ እንደሚገባ አቅጣጫ አስቀምጠዋል፡፡